ከኢትዮጵያ ወደ ህንድ ሊገባ የነበረ 3.1ኪሎ ወርቅ፣ ወደ ግብጽ የገቡት 2 የህዝባዊ አመጹ ወጣቶች፣ ቢያንስ 3 የወያኔ ወታደሮች ሶማሊያ ውስጥ ተገደሉ

ፍኖተ ዴሞክራሲ የኢትዮጵያ አንድነት ድምጽ (ህዳር 12 ቀን 2016 ዓ. ም.) – ባለፈው ሳምንት አንዲት ኢትዮጵያዊት 3.1 ኪሎግራም የሚመዝን ወርቅ ና $ 10, 000 ዶላር ጥሬ ገንዘብ እንዲሁም የሌሎች አገሮች ገንዝብ ኖቶች ይዛ ወደ ህንድ ለመግባት ስትሞክር ዴሊሂ የኢንድራ ጋንዲ ዓለም አቀፍ አውሮፕላን ማረፊያ ላይ በፈታሾች ተይዛ የታሰረች መሆኑ ተዘግቧል። የህንድ ባለስልጣኖች በሰጡት መግለጫ ግለሰቧ ከሁለት ወር በፊት ተመሳሳይ ሙከራ ስታደርግ ተያዛ በዋስ የተለቀቀች መሆኑን አስታውሰው በአሁኑ ወቅት የያዘቻቸው ንብረቶች በሙሉ የተያዙ መሆናቸውንና እሷም ወደ እስር ቤት የተላከች መሆኑን ገልጸዋል። ባለፈው ዓመት በተለያዩ የአገሪቱ ክፍሎች እየተካሄዱ የነበሩትን ሕዝባዊ አመጾች በመሸሽ በርክት ያሉ የወያኔ ባለስልጣኖች የዘረፉትን ሀብት በተለያዩ መንገዶች ሲያስወጡ የነበሩ መሆናቸው የሚታወቅ ሲሆን በህንድ ባለስልጣኖች በቁጥጥር ስር የዋለችው ሴት ምናልባት ከወያኔ ባለስልጣኖች መካከል አንዷ ወይም የነሱ ተባባሪ ልትሆን ትችላለች የሚለው ግምት እየተሰጠ ነው።

#ባለፈው መስከረም ወር በቢሸፍቱ በተደረገው የኢሬቻ በዓል ላይ ከመድረኩ መነጋገሪያውን በመቀማት ወያኔ ይወረድ ይቀበር (Down1 Down Weyane) በማለት መፈክር ሲያሰማ የነበረው ወጣትና እንዲሁም እንዲሁም ቀደም ብሎ በማስተር ፕላን ስም የአዲስ አበባ መስፋፋት በመቃወም በተደረጉ ሰልፎች እጆቹን በማውጣት ማስተር ፕላኑን ተቃወሙ ( Say No to Master plan) የሚል መፈክር ሲያሰማ እና ሰልፈኛውን ሲያስተባር የቆየው ወጣት ሁለቱም በአንድ ላይ በግብጽ ዋና ከተማ ካይሮ ውስጥ መገኘታቸው ታወቀ። የሁለቱ ወጣቶች ደህንነት ለረዥም ጊዜ ዜጎችን ሲያስጨንቅ የነበረ ቢሆንም ሰሞኑን ሶሻል ሚዲያ በተሰራጨ ፎቶግራፋቸው አማካይነት ካይሮ ውስጥ የሚገኙ መሆናቸውን ለማወቅ ተችሏል።

#ባለፈው ቅዳሜ ኅዳር 10 ቀን 2009 ዓ.ም. በሱማሊያ ደቡብ በምትገኘው በኪስማዩ ከተማ አጠገብ የተቀበረ ቦምብ ፈንድቶ ቢያንስ ሶስት የወያኔ ወታደሮች የተገደሉ መሆናቸው ታውቋል። በአፍሪካ ህብረት የሰላም አስከባሪ ኃይል ስር የተሰማሩት እነዚህ ወታደሮች ሊገደሉ የቻሉት የሚሄዱበት ተሽከርካሪ በርቀት መቆጣጠርያ አማካይነት በፈነዳ ቦምብ ጉዳት ስለደረሰበት ነው ተብሏል። ከቦምቦ ጉዳት በኋላ በኮንቮይ መልክ ይንቀሳቀስ የነበረው ጦር ኪስማዩ ወደ ሚገኘው የጦር ሰፈር ተመልሷል።